Alsae degefe
Alsae degefe
04/11/2022
ደቡብ አፍሪካ ውስጥ በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከዓመታት በፊት አንድ ቤተ ክርስቲያን መሠረቱ:: ይህንን የጥቁሮች ቤተ ክርስቲያን በሥራቸው ለማድረግ ብዙ የእምነት ተቋማት መረባረብ ጀመሩ:: የሮማ ካቶሊክ ፣ የአንግሊካን ወዘተ በብዙ ቁጥር የተሰባሰቡትን ደቡብ አፍሪካውያን ለመማረክ ያላደረጉት ጥረት አልነበረም::
ምእመናኑ ግን ለማንም እጅ አልሠጡም:: ለሚጠይቃቸው ሁሉ መልሳቸው አንድ ነበረ::
"እኛ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ነን"
በኢትዮጵያ ስም ለመሰብሰባቸው ምክንያቱ "ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች" የሚለው የንጉሥ ዳዊት መዝሙርና የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ታሪክ ነበረ:: ምንም እንኳን ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ እውቅና ባይሠጣቸውም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን በፍቅር እየጠበቁ ተሰብስበው መጽሐፍ ቅዱስን መማራቸውን ቀጠሉ::
ድንገት ግን የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ላይ ለመካፈል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የካሪቢያን ሊቀ ጳጳስ የነበሩትና ቦብ ማርሌይን (ብርሃነ ሥላሴ) ጨምሮ በሺህዎች የሚቆጠሩ ጃማይካዊያንን በማጥመቅ የሚታወቁት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ወደ ደቡብ አፍሪካ ይመጣሉ:: ይህንን የሰሙት የደቡብ አፍሪካ ምእመናን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ልጆችዋን ትሰብስበን ብለው ብፁዕነታቸውን ይጠይቃሉ:: በዚህ ልባቸው የተነካው አቡነ ይስሐቅም ከምእመናኑ ጋር ሰንብተው በቂ ትምህርት ከሠጡ በኋላ ከመካከላቸው በዕድሜ የበሰሉትንና በበጎ ሥራቸው የተመሰገኑትን በሐዋርያዊው ትውፊት መሠረት ክህነት ሾመው ሕዝቡን ቀድሰው አቁርበው ተመለሱ:: በዚህም የደቡብ አፍሪካውያን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተወለደች::
በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዘመነ ፕትርክና ደግሞ ቅዱስነታቸው ሥፍራውን በአካል ተገኝተው ምእመናኑን በመጎብኘትና በመደገፍ ከልጆቻቸውም ዲያቆናትን በመሾም የተተከለችውን ቤተ ክርስቲያን የተንከባከቡአት ሲሆን በሥፍራው በሊቀ ጵጵስና ተሹመው ባገለገሉት በብፁዕ አቡነ ያዕቆብም የምእመናኑና የካህናቱ ቁጥር በዝቶ ቅዳሴ በራሳቸው እስከመቀደስና ምሥጢራትን ሁሉ እስከመፈጸም ደርሰዋል:: "ይስሐቅ ተከለ ያዕቆብ አጠጣ እግዚአብሔር ያሳድግ ነበረ" ነው ነገሩ::
ደቡብ አፍሪካውያኑ ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እቅፍ እስኪገቡ ድረስ እጅግ ብዙ ዋጋ ከፍለዋል:: በወቅቱ ብዙ ዋጋ ከከፈሉ ሰዎች መካከል ፋዘር ዴሊዛ አንዱ ናቸው:: በደቡብ አፍሪካ የመጀመሪያዎቹ ካህናት ውስጥ አንጋፋ የሆኑት ፋዘር ዴሊዛ ከገንዘብ ሥጦታ ማባበያ እስከ ግድያ ሙከራ ድረስ ታግሠው ቤተ ክርስቲያንዋን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እንድትሆን ያስቻሉ ብርቱ ካህን ነበሩ:: እኚህ ውድ የቤተ ክርስቲያን አባት በዚህ ሳምንት ወደ አምላካቸው እንደተጠሩ ሰማሁ::
በደቡብ አፍሪካ በአገልግሎት ላይ በቆየሁ ጊዜ ከፋዘር ዴሊዛ ጋር የማይረሳ ጊዜ አሳልፌያለሁ:: ፋዘር ዴሊዛ እጅግ ጨዋታ አዋቂ ፣ በጣም የሰላ አእምሮ ያላቸው ፣ ጸሎተኛና ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቆጩና የሚቆረቆሩ አባት ነበሩ:: የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች የደቡብ አፍሪካ ምእመናንን በመንከባከብና በማስተማር ዙሪያ ብዙ ዕዳ እንዳለብን አበክረው ይናገሩ ነበር::
የጆሃንስበርግ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ አገልግዬ ስጨርስ ፋዘር ዴሊዛ "የዛሬው ትምህርት ምን ነበር?" ብለው አስጨንቀው ሙሉ ትምህርቱን በትርጉም ያስደግሙኝ ነበር:: ሰምተውት የማያውቁትን ነገር ሲሰሙ "ይሄን እስካሁን መስማት አልነበረብኝም? እናንተ እኮ ትጠየቃላችሁ" ይሉ ነበር::
ፋዘር ደሊዛ ከግሪካዊትዋ የመጻሕፍት ወዳጅ ጋር ያስተዋወቁኝን ቅጽበትም አልረሳውም:: አንድ ጠዋት የEastern Orthodx book store በGoogle map ላይ ፈልጌ አገኘሁ አልኳቸው:: እሳቸው ግን "ጊዜህን አታቃጥል" አሉና ዝም አሉ:: አልሰማ ብዬ ስንከራተት ውዬ የተባለው ሥፍራ ስደርስ አቧራ የቃመ የተዘጋ ቤት ሆኖ አገኘሁት:: በማግስቱ ሳገኛቸው ፈገግ እያሉ "የሔድክበት ተሳካልህ" አሉኝ::
እየተበሳጨሁ ነገርኳቸው:: እሳቸውም እየሳቁ "ነገርኩህ እኮ ከእኔ ይልቅ ጉግልን እንዴት ታምናለህ?" አሉ::
ከሳምንት በኋላ በጠዋት መጥተው ቀሰቀሱኝ:: (ተቀስቅሶ መነሣት እንደማልወድ ደጋግሜ ብነግራቸውም ፋዘር ዴሊዛ አልሰሙኝም:: "እባክዎን አያንኳኩ" ብዬ ቃል አስገብቻቸው እሺ ብለው በማግሥቱ መጥተው ሞቅ ባለድምፅ በር ላይ "እእህህህምምምም እህህህምምም" ብለው የቀሰቀሱኝን አልረሳውም:: ተበሳጭቼ ስጠይቃቸው "አያንኳኩ ነውያልከኝ አላንኳኳሁም" ብለው ሳልፈልግ አስቀውኛል:)
ያን ቀን በጠዋት ቀስቅሰው አንዲት ግሪካዊት ጋር አስተዋወቁኝ:: በቤትዋ ብዙ መጻሕፍት የምትሰበስብ ነበረች:: በግዢም በሥጦታም ብዙ ነገር አገኘሁ:: መጻሕፍት ጭነን ስንወጣ ፋዘር ዴሊዛ "Who ya gonna believe, Me or your Google map?" ብለው ቀለዱ::
ፋዘር ዴሊዛ ገንዘብ የሚያጠራቅሙባት ትንሽ ሳጥን ነበረቻቸው:: ለምን እንደሆነ ጠየቅኳቸው:: የክህነት አባታቸውን የአቡነ ይስሐቅን መቃብር የመጎብኘት እቅድ እንዳላቸው ነገሩኝ:: እኔም ትንሽ አዋጣሁ:: ከደቡብ አፍሪካ መልስ በወራት ልዩነቶች ይደውሉልኝ ነበር:: እኚህ ድንቅ አባት በክብር አርፈዋል:: መቃብራቸውን ለማየት ያልተሳካላካቸው መንፈሳዊ አባታቸውን አቡነ ይስሐቅንም በአጸደ ነፍስ ያገኙአቸዋል:: ዕረፍተ ነፍስ ይሥጥልን:: ለመንፈሳዊ ልጆቻቸው ሁሉ መጽናናትን ያድልልን::
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጥቅምት 2015 ዓ.ም.
አዲስ አበባ ፤ ኢትዮጵያ
ፎቶ:- 2006 ዓ.ም. ከአባታችን ጋር የተነሣሁት ነው::
30/10/2022
በአዲሱ ኪዳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከበሮ ሲሰራ በምሳሌ ነው ይኸውም ምሳሌ ጌታችን እኛን ለማዳን የከፈለውን ዋጋ የደረሰበትን እትራት በጥቂቱም ቢሆን ገላጭ እንዲሆን ተደርጎ ነው ።
30/10/2022
https://www.facebook.com/100018732784016/posts/1114441669190249/
+ ጌታ ሆይ ይህን ውኃ ሥጠኝ +
ሳምራዊትዋ ሴት በጠራራ ፀሐይ ውኃ ልትቀዳ እንስራዋን ይዛ ከጉድጓድ አጠገብ ተቀምጣለች፡፡ በጠዋት ወይም በማታ ውኃ መቅዳት ስትልችል ፀሐይ አናት በሚበሳበት በስድስት ሰዓት መምጣት እንዴት ልትመርጥ ቻለች? ከጎረቤቶችዋ ጋር እየተጫወተች አብራ ቀድታ መመለስ አትችልም ነበር? ብቻዋን ለመቅዳት ለምን ፈለገች? ከሰው ፀሐይ ያስመረጣት ምንድነው? ዝርዝሩን እርስዋ ናት የምታውቀው፡፡
አምስት ባሎች የነበሩዋት እና አሁንም ባልዋ ካልሆነ ሰው ጋር የምትኖር ሴት መሆንዋ ግን ተጽፎአል፡፡ ለብዙ ወንዶች ሚስት በሆነች ቁጥር ስለራስዋ የሚኖራት ግምት እየወረደ መምጣቱ አይቀርም፡፡ በተደጋጋሚ አልሳካ ባላት ትዳር ምክንያት ልብዋ እየቆሰለ ተስፋ እየቆረጠች ሁሉን ነገር እየጠላች መምጣትዋ አይቀርም፡፡ እርስዋ ስላልተሳካው ትዳርዋና አሁንም ባልዋ ካልሆነ ሰው ጋር ስለመኖርዋ ሰዎች የሚያወሩት ግን ብዙ ነው፡፡ የእርስዋን ሕመም ሳይረዳ እንደ ርካሽ የሚቆጥራት ፣ ዝሙተኛ አድርጎ የሚያስባት ፣ ዕድለ ቢስ አድርጎ የሚፈርጃት በንቀት በአሽሙር ባለ አምስት ባሎች አድርጎ የሚነቁራት ሰው አይጠፋም፡፡ በግልጥ ባይነግሯትም በአስተያየት በአነጋገር የሚያሳቅቋት አይጠፉም፡፡ ስለዚህ ከሰው አፍ ፀሐይ ይሻለኛል ብላ መጣች፡፡ ሰዎች በነገር ከሚጠብሱኝ በፀሐይ ብትጠብሰኝ ይሻለኛል ብላ በበረሃማው ምድረ በዳ በአጉል ሰዓት ይህች ተስፋ ያጣች ምስኪን ውኃ ልትቀዳ ሔደች፡፡
“ኢየሱስም በሰማርያ ሊያልፍ ግድ ሆነበት” እርግጥ ነው ከይሁዳ ወደ ገሊላ ለመሔድ በሰማርያ ማለፍን መልክዓ ምድሩ ያስገድዳል፡፡ ክርስቶስ ግን ግድ የሆነበት በመልክዐ ምድሩ ብቻ አልነበረም፡፡ የጠፋውን የሰው ልጅ ሊያድን የመጣው መድኃኒት እርሱ ነውና አንዲትን በፀሐይ የምትለበለብ ነፍስ ፍለጋ ሊሔድ ግድ ሆነበት፡፡ ከሰው ሸሽታ ምድረ በዳ የመረጠችውን ተስፋ የቆረጠች ሴት የአሕዛብ ተስፋ ክርስቶስ ሊፈልጋት ተገኘ፡፡
ወደ እርስዋ ቀርቦ ውኃ አጠጪኝ አላት ፤ አባ ጊዮርጊስ ‘’አንተ የሕይወት ውኃ ስትሆን ከሳምራዊትዋ ሴት ውኃን ለመንህ ‘’ እንዳለ የሕይወት ውኃ ክርስቶስ ውኃ ለመናት፡፡ እርሱ የተጠማው ውኃ ሳይሆን የእርስዋን ነፍስ ነበረ፡፡
እርስዋም አንተ አይሁዳዊ ስትሆን ሳምራዊት ከምሆን ከእኔ ውኃ ትለምናለህ? አለችው፡፡ እንዲህ ነው ነገሩ፡፡ የቆሰለች ነፍስ ስለ ዘር ታወራለች፡፡ ተስፋ የቆረጠች ነፍስ የዘር ጉዳይ ሲሆን ልሳንዋ ይከፈታል፡፡ ውኃ ለማጠጣት ዘር መጠየቅን ምን አመጣው፡፡ ውኃው አይሁዳዊ ነው? ወይንስ ሳምራዊ? ውኃ ጠማኝ የሚል ሁሉ ውኃ ይገባዋል እንጂ ዘሩ አይጠየቅም፡፡ እርስዋ ግን ጠየቀችው፡፡ በእርግጥ ይህች ሳምራዊት ሴት ይህን ጥያቄ የጠየቀችው ክርስቶስ መሆኑን ከማወቅዋ በፊት ነበር፡፡ ክርስቶስ መሆኑን ካወቀች በኋላ ግን ስለ አይሁዳዊነትና ስለ ሳምራዊነት ስትናገር አልተሰማችም፡፡ ‘’አንተ አማራ ስትሆን ጉራጌ ከምሆን ከእኔ ውኃ ለምን ትለምናለህ?’’ ‘’አንቺ ኦሮሞ ስትሆኚ ትግሬ ከምሆን ከእኔ እንዴት ውኃ ትለምኛለሽ?’’ በሚል ጥያቄ ሀገሩን ያጨናነቁተ ክርስቶስን ያወቁ ክርስቲያኖች መሆናቸው ግን ልብን የሚሰብር እውነታ ነው፡፡ በዚህ ጠባያችን እንደ ክርስቲያን ሳንኖር እንደ ክርስቲያን ልንሞት መሆኑ ምንኛ ያሳዝናል?
ጌታችን የሴቲቱን የዘር ጥያቄ እንዳልሰማ አለፈውና ‘’ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መሆኑን ብታውቂ የሕይወትን ውኃ እንዲሰጥሽ ትለምኚው ነበር’’ አላት፡፡ አሁንም የተጠማው የእርስዋን መመለስ ነውና እርስዋ ያነሳችውን ርእስ ሳያነሳ የውኃ ጥያቄውን ቀጠለ፡፡ ውኃን የፈጠረ ጌታ የሴቲቱን በተሰበረ ልብ የሚፈስስ ዕንባ ተጠምቶ ውኃ ለመናት፡፡
‘’ጌታ ሆይ መቅጃ የለህም ጉድጓዱ ጥልቅ ነው’’ አለችው፡፡ እንዴት ያለ ንግግር ነው፡፡ የነፍስዋን መመለስ ለተጠማው ጌታ ይህ ምላሽ እንዴት ከባድ ነው?
እውነት ጌታ መቅጃ የለውም? እውነትስ ጉድጓዱ ጥልቅ ነው? አዎ ልክ ነው የለውም፡፡
ጌታ ሆይ መቅጃ የለህም ፤ ጉድጓዱም ትልቅ ነው፡፡ ብዙ ተስፋ የቆረጡ ነፍሳትን ፣ ወደ አንተ መመለስ የሚሹ አንተም የተጠማሃቸው ነፍሳት በጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ወድቀዋል፡፡ የገቡበት አዘቅት ጥልቅ ነው ፤ በጥላቻ ፣ በክፋት ፣ በብዙ ተስፋ ማጣት ጉድጓድ ውስጥ የገቡ አንተ የተጠማሃቸው ነፍሳት ብዙ ናችው፡፡ ነገር ግን ሳምራዊትዋ እንዳለችው ከጉድጓዱ ማውጫ መቅጃ የለህም፡፡ ካለህ እስቲ ንገረን፡፡ ሕዝብህን ከጉድጓድ ውስጥ የሚያወጣ የአንተን ፈቃድ የሚፈጽምልህ አገልጋይ አለህ? ሁሉም ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ የቀረ አይደለምን? ራሱ መቅጃ የሚፈልግ መቅጃማ ሞልቶሃል? እንደ ኢሳይያስ ዘመን ‘’ማንን እልካለሁ’’ ብለህ ብትጣራ ይሻልሃል እንጂ መቅጃስ የለህም፡፡ ወይ ሱራፊን ልከህ በእሳት ፍሕም ተኩሰህ ካላነጻኸን በቀር መቅጃ የለህም፡፡
ሴቲቱ የያዕቆብን አምላክ ክርስቶስን ‘አንተ ከያዕቆብ ትበልጣለህ?’’ አለችው፡፡ ተስፋ የቆረጠ ሰው ንግግሩ ሻካራ ነው፡፡ ‘’አንተ ከማን ትበልጣልህ? ከእገሌ ተሽለህ ነው?’’ የሚሉ ቃላት ነፍሱ የቆሰለ ሰው ንግግሮች ናቸው፡፡ ክርስቶስ አላስቀየማትም፡፡ አመል ያሳጣት የተመረረችበት ኑሮዋ እንደሆነ ያውቃል፡፡ “የተጎዱ ሰዎች ሰውን ይጎዳሉ” (hurt people hurt people) እንደሚባለው መጉዳትዋ ከመጎዳት ነውና ክብሬን ላስጠብቅ ሳይል ታገሳት፡፡ ባል የለኝም ስትል እንኳን ‘’እውነት ተናገርሽ’’ አሁን ያለው ባልዋ ባለመሆኑ እንዲህ እንዳለች አድርጎ ከሐሰትዋ ውስጥ እውነት አወጣላት፡፡
የተቀጠቀጠ ሸንበቆ የማትሰብረው የሚጤስ ጧፍ የማታጠፋው ትሑት አምላካችን ሆይ ክፉ ንግግሮቻችን የሚፈልቁት ከክፉ አኗኗራችን ነውና እባክህን እኛንም ታገሰን፡፡ ኢትዮጰያውያን ተሳዳቢዎች ፣ ዘረኞች ፣ ነውረኞች ያደረገን የተበላሸ ሕይወታችን ነውና ይቅር በለን፡፡ በመጥፎ ንግግሮቻችን የምናሳዝንህ ፣ በእርስ በእርስ መበላላት የምናስከፋህ ሳምራዊትዋ ሴት ባሎች እንደተፈራረቁባት ብዙ ፖለቲከኞች ተፈራርቀውብን ፣ ትዳር አልሳካ ብሎን ነውና እርስዋን እንደታግስህ ታገሰን፡፡
ሴቲቱን ጌታ ታግሶ የጎደላትን ሞላላት፡፡ ‘’እኔ ከምሠጠው ውኃ የሚጠጣ ለዘላለም አይጠማም ‘’ አላት፡፡ እርስዋም ‘ጌታ ሆይ እንዳልጠማ ውኃም ልጠጣ ወደዚህ እንዳልመጣ ይህን ውኃ ስጠኝ’’ አለችው፡፡ ይህ ውኃ ‘የሕይወት ውኃ እኔ ነኝ’’ ያለው ክርስቶስ ራሱ ነው፡፡ ሴቲቱም እርሱ መሆኑን ስታውቅ እንስራዋን ጣለች፡፡ እርሱን ካገኘች በኋላ እንደማትጠማ እርግጠኛ ነበረች፡፡
ወዳጄ ሆይ እንደ ሳምራዊትዋ ሴት መመላለስ የሰለቸህ መንገድ የለም? ስትጠጣው አሁንም ጨምር የሚያሰኝህ የማይቆርጥ ጥም የለህም? ልትቀዳ የምትመላለስበት ጉድጓድስ የለም? ሁለተኛ አልሔድም ብለህ ዝተህ የምሔድበት ቦታ የለም? ሁለተኛ አልጠጣውም ብለህ የምትጠጣው ሁሌ የሚጠማህ ውኃ ምንድር ነው?
ሁሌ የሚጠማህ መላቀቅ እየፈለግህ ያልተውከው ፣ ዞረህ የምትሔድበት ፣ ታጥቦ ጭቃ ፣ አድሮ ቃሪያ ፣ ከርሞ ጥጃ የሆንህበት ልማድ የለህም? ክርስቶስ ቦታውንም ውኃውንም ያውቀዋል፡፡ ከዚህ መገላገል ከፈለግህ እንደ ሳምራዊትዋ ሴት እንዲህ በለው፦
‘ጌታ ሆይ እንዳልጠማ ውኃም ልጠጣ ወደዚህ እንዳልመጣ ይህን ውኃ ስጠኝ’’
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 28/ 2012 ዓ ም
ሜልቦርን አውስትራሊያ ተጻፈ
ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ዘንድ ጸልዩ! ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like እና Share ያድርጉ
FB: https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
Telegram: https://t.me/deaconhenokhaile
Instagram: https://www.instagram.com/p/CBnMF0nnhcQ/?igshid=549jvl607bv4
Youtube: https://www.youtube.com/channel/UCOaVsWC05aUjeqIEW3fWj7g
Click here to claim your Sponsored Listing.
Category
Telephone
Website
Address
الرياض, السعودية
Riyadh
12211